በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘እኔ ይሖዋ አምላካችሁ ቅዱስ ነኝ’

‘እኔ ይሖዋ አምላካችሁ ቅዱስ ነኝ’

ወደ አምላክ ቅረብ

‘እኔ ይሖዋ አምላካችሁ ቅዱስ ነኝ’

ዘሌዋውያን ምዕራፍ 19

“ይሖዋ አምላክ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ነው።” (ራእይ 4:8) በዚህ መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ይሖዋ ቅዱስ እንደሆነ ይኸውም የላቀ የንጽሕና ደረጃ እንዳለው ይናገራል። አምላክ ከኃጢአት ፈጽሞ የራቀ ሲሆን ኃጢአት በማንኛውም መንገድ ሊያጎድፈው አይችልም። ታዲያ ይህ ሲባል ፍጹማን ያልሆኑ ሰዎች እጅግ ቅዱስ ከሆነው አምላክ ጋር ዝምድና መመሥረት አይችሉም ማለት ነው? በጭራሽ እንዲህ ማለት አይደለም! እስቲ በዘሌዋውያን ምዕራፍ 19 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘውን ተስፋ የሚሰጥ ሐሳብ እንመልከት።

ይሖዋ ለሙሴ፣ “ለመላው የእስራኤል ሕዝብ ጉባኤ እንዲህ ብለህ ተናገራቸው” አለው። ይሖዋ ቀጥሎ የተናገረው ሐሳብ እያንዳንዱን እስራኤላዊ የሚመለከት ጉዳይ ነበር። ሙሴ ለሕዝቡ እንዲናገር የታዘዘው ምን ነበር? አምላክ በመቀጠል እንዲህ አለ፦ ‘እንዲህ ብለህ ተናገራቸው “እኔ ይሖዋ አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ።”’ (ቁጥር 2 NW) እያንዳንዱ እስራኤላዊ ቅዱስ እንዲሆን ይጠበቅበት ነበር። እዚህ ላይ ይሖዋ ሕዝቡ ቅዱስ ቢሆን ጥሩ እንደሆነ ሐሳብ እያቀረበ ሳይሆን ትእዛዝ እየሰጠ ነው። ታዲያ አምላክ ከሰው አቅም በላይ የሆነ ነገር እንዲያደርጉ እያዘዛቸው ነበር?

እዚህ ላይ ልብ ልንለው የሚገባ አንድ ነገር አለ፦ ይሖዋ የራሱን ቅድስና የጠቀሰው፣ ሰዎች ሊደርሱበት የሚገባቸውን የቅድስና መሥፈርት ለመግለጽ ሳይሆን ለሰጣቸው ትእዛዛት ምክንያት የሆነው ነገር ምን እንደሆነ ለማሳወቅ ነው። በሌላ አባባል ይሖዋ ፍጹማን ያልሆኑትን እስራኤላውያን አገልጋዮቹን እሱ ያለበት የላቀ የቅድስና ደረጃ ላይ እንዲደርሱ እየነገራቸው አልነበረም። ይህ ፈጽሞ የማይቻል ነገር ነው። “እጅግ ቅዱስ” የሆነው ይሖዋ በቅድስናው የሚተካከለው የለም። (ምሳሌ 30:3 NW) ያም ሆኖ ይሖዋ ቅዱስ ስለሆነ አገልጋዮቹም ፍጹማን ያልሆኑ ሰዎች ሊደርሱበት የሚችሉትን ያህል ቅዱሳን እንዲሆኑ ይጠብቅባቸዋል። ቅዱሳን መሆናቸውን ማሳየት የሚችሉት በየትኞቹ መንገዶች ነው?

ይሖዋ፣ አምላኪዎቹ ቅዱሳን እንዲሆኑ ትእዛዝ ከሰጠ በኋላ በሙሴ በኩል እያንዳንዱን የሕይወታቸውን ዘርፍ የሚመለከቱ መመሪያዎችን ሰጣቸው። እያንዳንዱ እስራኤላዊ የሚከተሉትን ከሥነ ምግባር ጋር የተያያዙ መመሪያዎች መታዘዝ ነበረበት፦ ለወላጆቹና ለአረጋውያን ተገቢውን አክብሮት እንዲሰጥ (ቁጥር 3, 32)፣ መስማት ወይም ማየት ለተሳናቸውና ለድኾች አሳቢነት እንዲያሳይ (ቁጥር 9, 10, 14)፣ ከሌሎች ጋር ባለው ግንኙነት ሐቀኛና የማያዳላ እንዲሆን (ቁጥር 11-13, 15, 35, 36) እንዲሁም ባልንጀራውን እንደ ራሱ እንዲወድ ይጠበቅበት ነበር። (ቁጥር 18) አንድ እስራኤላዊ እነዚህንም ሆኑ ሌሎቹን ትእዛዛት በመጠበቅ ‘ለአምላኩ ቅዱስ መሆኑን’ ማሳየት ይችላል።—ዘኍልቍ 15:40

በዘሌዋውያን 19:2 ላይ ስለ ቅድስና የተሰጠው ትእዛዝ፣ ስለ ይሖዋ አምላክ አስተሳሰብና ነገሮችን ስለሚይዝበት መንገድ ጥልቅ ማስተዋል እንድናገኝ ይረዳናል። አንደኛ ነገር ከይሖዋ ጋር የቅርብ ወዳጅነት ለመመሥረት ቅዱስ ምግባር በማሳየት ረገድ እሱ የሚጠብቅብንን ለማሟላት የተቻለንን ሁሉ ማድረግ እንደሚያስፈልገን እንማራለን። (1 ጴጥሮስ 1:15, 16) ሁልጊዜ በእነዚህ መሥፈርቶች በመመራት ከሁሉ በተሻለው የሕይወት ጎዳና ላይ መጓዝና ደስታ ማግኘት እንችላለን።—ኢሳይያስ 48:17

በተጨማሪም ቅዱስ ስለ መሆን የተሰጠው ትእዛዝ ይሖዋ በአገልጋዮቹ እምነት እንዳለው ያሳያል። ይሖዋ በጭራሽ ከምንችለው በላይ እንድናደርግ አይጠብቅብንም። (መዝሙር 103:13, 14) ሆኖም በእሱ አምሳል የተፈጠርን እንደመሆናችን መጠን በአንጻራዊ ሁኔታም ቢሆን የቅድስናን ባሕርይ የማሳየት ችሎታ እንዳለን ያውቃል። (ዘፍጥረት 1:26) ታዲያ ይህን ማወቅህ ቅዱስ አምላክ ወደ ሆነው ወደ ይሖዋ ይበልጥ ለመቅረብ የምትችለው እንዴት እንደሆነ ለመማር ያለህን ፍላጎት አልጨመረልህም?

[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በተፈጥሯችን የቅድስናን ባሕርይ የማሳየት ችሎታ አለን