በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትንቢት 3. በሽታ

ትንቢት 3. በሽታ

ትንቢት 3. በሽታ

“ሰዎች . . . አስከፊ በሆኑ በሽታዎች ይሠቃያሉ።”​—ሉቃስ 21:11 ኮንቴምፖራሪ ኢንግሊሽ ቨርሽን

● በእርስ በርስ ጦርነት በምትታመስ አንዲት የአፍሪካ አገር ውስጥ የጤና መኮንን ሆኖ የሚሠራው ቦንዛሊ፣ ማርበርግ በተባለ ቫይረስ እያለቁ ያሉትንና እሱ ባለበት ከተማ የሚኖሩትን የማዕድን ሠራተኞች ለመታደግ አቅሙ የፈቀደውን ሁሉ እያደረገ ነው። * እርዳታ ለማግኘት በአንድ ትልቅ ከተማ ላሉ ባለሥልጣናት አቤት ቢልም መልስ ሳያገኝ ቀረ። በስተመጨረሻ ከአራት ወራት በኋላ ጥያቄው ምላሽ ቢያገኝም ቦንዛሊ ግን ሕይወቱ አልፎ ነበር። ማርበርግ የያዛቸውን የማዕድን ሠራተኞች ለማዳን በሚያደርገው ጥረት በሽታው ተጋብቶበት ነበር።

እውነታው ምን ያሳያል? በሰው ዘር ላይ እልቂት እያስከተሉ ካሉት በሽታዎች መካከል በታችኛው የመተንፈሻ አካላት ላይ የሚያጋጥሙ እንደ ሳንባ ምች ያሉ በሽታዎች፣ የተቅማጥ በሽታ፣ ኤች አይ ቪ/ኤድስ፣ ሳንባ ነቀርሳና ወባ ይገኙባቸዋል። በቅርቡ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ብቻ እነዚህ አምስት ዓይነት በሽታዎች 10.7 ሚሊዮን የሚገመቱ ሰዎችን ሕይወት ቀጥፈዋል። ስሌቱን በሌላ መንገድ ስናስቀምጠው እነዚህ በሽታዎች ዓመቱን ሙሉ ያለማቋረጥ በየሦስት ሴኮንዱ የአንድ ሰው ሕይወት ቀጥፈዋል ማለት ይቻላል።

በተደጋጋሚ የሚሰነዘረው የተቃውሞ ሐሳብ ምንድን ነው? የዓለም ሕዝብ ብዛት እየጨመረ በመጣ ቁጥር በበሽታ የሚያዙትም ሰዎች ቁጥር እየጨመረ መሄዱ አይቀርም። ገና ብዙ ሰዎች ይታመማሉ።

ይህ የተቃውሞ ሐሳብ ትክክል ነው? የዓለም ሕዝብ ብዛት በአስደንጋጭ ፍጥነት ጨምሯል። ይሁን እንጂ የሰው ልጅ በሽታን በምርመራ ለይቶ የማወቅ፣ የመቆጣጠርና የማከም ችሎታውም የዚያኑ ያህል አድጓል። ታዲያ እንዲህ ከሆነ በሽታ በሰው ዘር ላይ የሚያደርሰው ችግር እየቀነሰ መምጣት አልነበረበትም? ሁኔታው ግን የተገላቢጦሽ ነው።

ምን ይመስልሃል? መጽሐፍ ቅዱስ አስቀድሞ በተናገረው መሠረት ሰዎች አስከፊ በሆኑ በሽታዎች እየተሠቃዩ እንዳሉ ይሰማሃል?

በሚሊዮን በሚቆጠሩ ሰዎች ላይ ከፍተኛ ጥፋት የሚያደርሱት የምድር ነውጦች፣ ረሃብና በሽታ እንደ ሰው ሊወቀሱ አይችሉም። ሌሎች በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ግን በመሰሎቻቸው መከራና ሥቃይ ይደርስባቸዋል፤ በአብዛኞቹ ላይ እንዲህ ያለ ጥቃት የሚያደርሱት አለኝታ ሊሆኗቸው የሚገቡ ሰዎች ናቸው። በዚህ ረገድ አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት የሚናገረውን ሐሳብ ልብ በል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.3 ማርበርግ ሄመሬጂክ ፊቨር፣ ከኤቦላ ጋር በሚዛመድ ቫይረስ የሚመጣ በሽታ ነው።

[በገጽ 6 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“በአንበሳ ወይም በሌላ አውሬ መበላት በጣም ዘግናኝ ነገር ነው፤ አስከፊ የሆነ በሽታ ውስጣችንን ሲበላውም ሆነ በዙሪያችን ያሉት ሰዎች እንዲህ ያለ ነገር ሲደርስባቸው መመልከቱም የዚያኑ ያህል እጅግ ዘግናኝ ነው።”​—ኤፔዲሚዮሎጂስት፣ ሚካኤል ኦስተርሆልም

[በገጽ 6 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

© William Daniels/Panos Pictures