በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትንቢት 6. ዓለም አቀፍ የስብከት ሥራ

ትንቢት 6. ዓለም አቀፍ የስብከት ሥራ

ትንቢት 6. ዓለም አቀፍ የስብከት ሥራ

“ይህ የመንግሥቱ ምሥራች . . . በመላው ምድር ይሰበካል።”​—ማቴዎስ 24:14

● ቫየቲያ የምትኖረው ቱአሞቱ ተብለው ከሚጠሩት እጅብ ብለው የሚገኙ የፓስፊክ ደሴቶች መካከል በአንዷ ውስጥ ነው። ቱአሞቱ 802,900 ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት ባለው ቦታ ላይ የተቀመጡ መሃላቸው ላይ ሐይቅ የሚገኝባቸው 80 ባለ ቀለበት ቅርጽ ደሴቶችን ያቀፈ ቢሆንም የሕዝቡ ብዛት 16,000 ብቻ ነው። ሆኖም የይሖዋ ምሥክሮች ቫየቲያ ወዳለችበት ደሴት በመሄድ እሷን እና የአካባቢዋን ሰዎች አነጋግረዋቸዋል። ለምን? ምክንያቱም የይሖዋ ምሥክሮች፣ ሰዎች የሚኖሩት የትም ይሁን የት ያሉበት ቦታ ድረስ ሄደው ስለ አምላክ መንግሥት የሚገልጸውን ምሥራች ሊያካፍሏቸው ስለሚፈልጉ ነው።

እውነታው ምን ያሳያል? የአምላክ መንግሥት መልእክት ወደ ሁሉም የምድር ማዕዘኖች እየደረሰ ነው። በ2010 ብቻ የይሖዋ ምሥክሮች በ236 አገሮች ምሥራቹን በማወጅ ከ1.6 ቢሊዮን በላይ ሰዓት አሳልፈዋል። ይህም ማለት እያንዳንዱ የይሖዋ ምሥክር በየቀኑ በአማካይ 30 ደቂቃ በስብከቱ ሥራ ላይ አሳልፏል ማለት ነው። የይሖዋ ምሥክሮች ባለፈው አሥር ዓመት ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስን ለማስተማር የሚረዱ ከ20 ቢሊዮን የሚበልጡ ጽሑፎችን በማተም አሰራጭተዋል።

በተደጋጋሚ የሚሰነዘረው የተቃውሞ ሐሳብ ምንድን ነው? የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት በሺህ ለሚቆጠሩ ዓመታት ሲሰበክ ኖሯል።

ይህ የተቃውሞ ሐሳብ ትክክል ነው? እውነት ነው፣ ብዙ ሰዎች መልእክቱ ምንም ይሁን ምን ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ሰብከዋል። ይሁን እንጂ አብዛኞቹ ይህን ያደረጉት አጭር ለሆነ ጊዜና ውስን በሆኑ አካባቢዎች ነው። በአንጻሩ ግን የይሖዋ ምሥክሮች በተደራጀ መልክ ዓለም አቀፍ የስብከት ዘመቻ እያካሄዱ ሲሆን መልእክቱንም በብዙ መቶ ሚሊዮን ለሚቆጠሩ ሰዎች ማዳረስ ችለዋል። የይሖዋ ምሥክሮች በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ እጅግ ኃያልና ጨካኝ ከሆኑት ድርጅቶች ከባድ ተቃውሞ እየደረሰባቸውም እንኳ በስብከቱ ሥራ በጽናት ቀጥለዋል። * (ማርቆስ 13:13) ከዚህም በላይ የይሖዋ ምሥክሮች የሚሰብኩት ተከፍሏቸው አይደለም። ከዚህ ይልቅ ጊዜያቸውን በፈቃደኝነት ይሰጣሉ እንዲሁም ሰዎች ጽሑፎቻቸውን እንዲወስዱ የሚጋብዙት በነፃ ነው። ሥራቸው ሙሉ በሙሉ የሚካሄደው በፈቃደኝነት በሚደረጉ ወዋጮዎች ነው።

ምን ይመስልሃል? “የመንግሥቱ ምሥራች” በመላው ዓለም እየተሰበከ እንደሆነ ይሰማሃል? የዚህ ትንቢት መፈጸም በቅርቡ አንድ የተሻለ ነገር እንደሚመጣ የሚጠቁም ይሆን?

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.6 ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት የይሖዋ ምሥክሮች የሚያሰራጯቸውን “ፌይዝፉል አንደር ትራያልስ፣” “ፐርፕል ትራያንግልስ” እና “ጀሆቫስ ዊትነስስ ስታንድ ፈርም ኧጌንስት ናዚ ኧሶልት” የተባሉትን ሦስት የቪዲዮ ፊልሞች ተመልከት።

[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

“ይሖዋ እስከፈቀደው ጊዜ ድረስ . . . ሰዎችን አግኝተን ለማነጋገር የሚያስችሉንን ዘዴዎች ሁሉ በመጠቀም የመንግሥቱን ምሥራች በቅንዓት መስበካችንን እንቀጥላለን።”​—የ2010 የይሖዋ ምሥክሮች የዓመት መጽሐፍ (እንግሊዝኛ)