በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችና ማብራሪያቸው

ዮሐንስ 14:27—“ሰላምን እተውላችኋለሁ”

ዮሐንስ 14:27—“ሰላምን እተውላችኋለሁ”

 “ሰላምን እተውላችኋለሁ፤ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ። እኔ ሰላም የምሰጣችሁ ዓለም በሚሰጥበት መንገድ አይደለም። ልባችሁ አይረበሽ፤ በፍርሃትም አይዋጥ።”—ዮሐንስ 14:27 አዲስ ዓለም ትርጉም

 “ሰላምን እተውላችኋለሁ፣ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ልባችሁ አይታወክ አይፍራም።”—ዮሐንስ 14:27 የ1954 ትርጉም

የዮሐንስ 14:27 ትርጉም

 በእነዚህ ቃላት አማካኝነት ኢየሱስ፣ ሐዋርያቱ መከራ ሲደርስባቸው ከልክ በላይ መጨነቅ እንደማይኖርባቸው በመግለጽ አጽናንቷቸዋል። ልክ እንደ እሱ፣ እነሱም በአምላክ እርዳታ ውስጣዊ ሰላማቸውን መጠበቅ ይችላሉ።

 ኢየሱስ ለሐዋርያቱ የተወላቸው ወይም የሰጣቸው ምን ዓይነት ሰላም ነው? ኢየሱስ የሰጣቸው ሰላሙን ማለትም እሱ ያገኘውን ሰላም ነው። ይህ ሰላም ከግጭት ወይም ከመከራ ነፃ መሆንን አያመለክትም። (ዮሐንስ 15:20፤ 16:33) ኢየሱስ ግፍ ቢደርስበትም፣ አልፎ ተርፎም ቢገደልም የአእምሮና የልብ ሰላም ነበረው። (ሉቃስ 23:27, 28, 32-34፤ 1 ጴጥሮስ 2:23) ይሖዋ a እንደሚወደውና እንደሚደሰትበት በማወቁ ውስጣዊ መረጋጋት ሊኖረው ችሏል።—ማቴዎስ 3:16, 17

 ኢየሱስ ለሐዋርያቱ ሰላም የሰጣቸው እሱም ሆነ አባቱ እንደሚወዷቸውና እንደሚደሰቱባቸው በማረጋገጥ ነው። (ዮሐንስ 14:23፤ 15:9, 10፤ ሮም 5:1) ኢየሱስ የአምላክ ልጅ መሆኑን በማመናቸው ያገኙት ይህ ሰላም ከፍርሃታቸውና ከጭንቀታቸው እንዲረጋጉ ረድቷቸዋል። (ዮሐንስ 14:1) ኢየሱስ ከዚያ በኋላ በአካል አብሯቸው ባይኖርም እንኳ የአምላክ ቅዱስ መንፈስ ድፍረትና ውስጣዊ ሰላም እንዲኖራቸው እንደሚረዳቸው ቃል ገብቶላቸዋል። (ዮሐንስ 14:25-27) የኢየሱስ ተከታዮች ይሖዋ እንደሚደሰትባቸውና እንደሚደግፋቸው ማወቃቸው ተፈታታኝ ሁኔታዎችን በድፍረት እንዲጋፈጡ ይረዳቸዋል።—ዕብራውያን 13:6

 ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ወቅት ሰዎች ሲገናኙ ‘ሰላም ለአንተ ይሁን’ የመባባል ልማድ ነበራቸው። (ማቴዎስ 10:12, 13) ሆኖም ኢየሱስ ሐዋርያቱ ሰላም እንዲያገኙ በመመኘት ብቻ አልተወሰነም፤ ከዚህ ይልቅ ሰላም ሰጥቷቸዋል። በተጨማሪም ኢየሱስ የሰጣቸው ሰላም፣ ዓለም b ሊሰጣቸው ከሚችለው ሰላም የተለየ ነው። ዓለም በዝምድና፣ በሀብት፣ በዝና ወይም በሥልጣን አማካኝነት መጠነኛ ሰላም ሊሰጠን ይችል ይሆናል። ሆኖም ኢየሱስ የሚሰጠው ሰላም በውጫዊ ነገሮች ላይ የተመካ አይደለም። ዘላቂ የሆነ ውስጣዊ ሰላም ነው።

የዮሐንስ 14:27 አውድ

 ኢየሱስ እነዚህን ቃላት ለታማኝ ሐዋርያቱ የተናገረው ከመሞቱ በፊት በነበረው ምሽት ላይ ነው። በዚያ ምሽት፣ ለሐዋርያቱ በቅርቡ እንደሚለያቸው ነገራቸው። (ዮሐንስ 13:33, 36) ይህም ሐዋርያቱን በጣም አሳዝኗቸው ነበር። (ዮሐንስ 16:6) በመሆኑም ኢየሱስ፣ እሱ በመሄዱ ማዘን የሌለባቸው ለምን እንደሆነ በመግለጽ አጽናናቸው።

 የኢየሱስ ቃላት በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖችንም ያበረታታሉ። እኛም ሰላም ሊኖረን ይችላል። (2 ተሰሎንቄ 3:16) የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ስንሆን እሱና አባቱ ይሖዋ እንደሚወዱንና እንደሚደሰቱብን ተምረናል። (ቆላስይስ 3:15፤ 1 ዮሐንስ 4:16) በመሆኑም ከልክ በላይ ልንጨነቅ አይገባም። ለምን? ምክንያቱም አምላክ ከጎናችን ነው።—መዝሙር 118:6፤ ፊልጵስዩስ 4:6, 7፤ 2 ጴጥሮስ 1:2

 የዮሐንስ መጽሐፍን አጠቃላይ ይዘት ለማየት ይህን አጭር ቪዲዮ ተመልከት።

a ይሖዋ የአምላክ የግል ስም ነው። (መዝሙር 83:18) “ይሖዋ ማን ነው?” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።

b በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “ዓለም” የሚለው ቃል ከአምላክ የራቁ ሰዎችን ያመለክታል።